(ዘ-ሐበሻ) በሚኒሶታ የሚገኘው የኦሮሞ ማህበረሰብ ነበር በቅድሚያ ይህን የኦሮሞ ተማሪዎችን ጥያቄ ለመደገፍ ሰላማዊ ሰልፍ የጠራው:: ይህን ተከትሎ በሚኒሶታ የሚገኘው የኢትዮጵያ ወጣቶች ንቅናቄ ሰልፉን እንደሚቀላቀልና ሰላማዊ ሰልፉን ደግፉ ከኦሮሞ ወንድም እና እህቶቹ ጋር እንደሚቆም መግለጫ አወጣ::
ይህ ሰልፍ በሰፊው ሚኒሶታ የአንድነት ምላሽ ማግኘቱን የተረዱና በኦሮሞ ሕዝብ ስም የሚነግዱ የሕወሓት መንግስት ተላላኪዎች ኢትዮጵያዊያኑን “በዚህ ሰልፍ ላይ የኢትዮጵያ ባንዲራም ሆነ ሌላ መል ዕክት ይዛችሁ መገኘት የለባችሁም.. ይህን ካደረጋችሁ ብጥብጥ ሊፈጠር ይችላል” የሚል ቅስቀሳ ማድረግ ጀመሩ:: ሆኖም እንዲህ ያለው ሕዝብ ሲገደል በአንድነት መቆም ሲገባ የሚያራርቅ ሥራ የሚሰሩት በኦሮሞ ሕዝብ ስም የሚነግዱ የሕወሓት መንግስት ተላላኪዎች መሆኑን የተረዱት ወገኖች ሰልፉን የኢትዮጵያን ባንዲራ ይዘው; የተላላኪዎቹን ማስፈራሪያ ወደጎን ትተው ጥያቄያችሁ ጥያቄያችን ነው በሚል ተቀላቅለውታል:: የሕወሓት መንግስት ተሸነፈ!!! ያሰበው ተንኮልና ሕዝብን ከሕዝብ የማራራቅ ተግባር በፍቅር ተሸንፏል::
ዛሬ በሚኒሶታ ስቴት ካፒቶል ደጃፍ ላይ ከቀኑ በ12 ሰዓት ነበር ይህ ሰላማዊ ሰልፍ የተጠራው:: ሰልፉ በተጠራበት ሰዓት ዝናብ እየዘነበ ነበር:: ባሃገር ቤት ሕዝብ ላይ የሕወሓት መንግስጥ ጥይት እያወረደ እኛ ዝናብ ቢወርድብን ልንፈራ ነው ወይ? ያሉ የሰልፉ ታዳሚዎች ስቴት ካፒቶሉን አጥለቀለቁት::
በሰልፉ ላይ የኦሮሞ ማህበረሰብ; የኦጋዴን ማህበረሰብ እና የእናትየው የኢትዮጵያ ባንዲራም ተውለብልቧል:: ለሕወሓት መንግስት በኦሮሚያ ምድር ላይ ንጹሃንን መገደሉን እንዲያቆም; በልማት ስም ገበሬዎችን ራቁቱን እያስቀረ መሬት መቸብቸቡን እንዲያቆም; ብሎም ያን ምድር ለቆ እንዲወጣ ተጠይቋል:: የአሜሪካ መንግስትም ከሕወሓት መንግስት ጋር እንዳይተባበር ሕዝቡ አምርሮ ጠይቋል::

ሰልፉ እየተደረገ ባለበት ወቅትም ወንድማማች የሆኑ ሕዝቦች በአንድ ላይ የተለያዩትን ባንዲራዎች በአንድ ላይ በመያዝ ለመጀምሪያ ጊዜ የአንድነት ፍቅር የተሞላበት ፎቶግራፎችን ሲነሱ ነበር:: በሚኒሶታ እንዲህ ያለውን ፍቅር እና አንድነት ለመመስረት ከፍተኛ የሆነ መስዋዕትነት እየተከፈለ ባለበት ሰዓት የሕወሃት መንግስት ተላላኪ የሆኑ ወገኖች በኦሮሞ ሕዝብ ስም ከኦሮሞ ሕዝብ ጎን እንቆማለን የሚሉትን ስም እየሰጡ የማንጓጠጥ ሥራ መስራታቸውን የማቆሚያ ጊዜው አሁን እንደሆነ ይህ ሰልፍ አሳይቶናል::
ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያውያን በሊቢያ ሲገደሉ አዝኖ እዚሁ ዛሬ ሰልፍ የተደረገበት ቦታ ላይ የወጡ ሁሉ ዛሬም እዚሁ ነበሩ:: በሞቱት ወገኖች ብናዝንም አንድነትና ፍቅራችንን በመመለሱ ደግሞ እንኮራለን::
በዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ ከሰልፈኞቹ እንደተነገረው የኦሮሞ ህዝብ ጥያቄ መብቱ እንዲከበርለት መጠየቅ እንጂ ከየትኛውም ብሄር ብሄረሰብ ጋር ለመጋጨት አይደለም:: አንዱን ከሌላው ለይቶ ከዚያ መሬት እንዲሰናበት መጠየቅ አይደለም::
Inga kommentarer:
Skicka en kommentar