የቀድሞው ጠ/ሚ/ር ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን የሰሞኑ ሕዝባዊ ቁጣ ለቤተሰቧና ለንብረቷ እንድታስብ እንዳደረጋት ገለጸች
(ዘ-ሐበሻ) በአንድ ወቅት “ደሃ ነኝ… ከዓለማችን የደሃ ሀገር መሪዎች መካከል እኛ አንደኞቹ ነን” ስትል የነበረችው የቀድሞው ሟች ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ባለቤት ወይዘሮ አዜብ መስፍን ሰሞኑን በኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች የተቀጣጠለውን ሕዝባዊ አመጽ ተከትሎ በገንዘቧና በቤተሰቧ ላይ ያሳደረውን ስጋቷን በፌስቡክ ገጿ ገለጸች::
ወ/ሮዋ በፌስቡክ ገጿ እንዳለችው “በሰሞኑ በሚሆነው ነገር በጣም በጣም የሚያሳዝን ነው። እኛ እንግዲህ አስራ ሰባት አመት ትግል ቦኅላ ለዚህ ድል በቅተን ደርግን ገርስሰን ለመላው ኢትዮጵያዊ ዲሞክራሲ ያለባት አገር መስርተናል። እና መለስ ልጅነቱን በሙሉ የለፋበትን አላማ ዛሬ በዚህ ብጥብጥ ባነሱ አደገኛ ቦዘኔዎች ከልማት ታቅበን መቀመጥ በጣም ያሳዝናል በእውነቱ። ስራ አቁሞ ሰልፍ ሲሰለፉ መዋል ምን ይባላል? ብንሰራ አይሻልም? እንደ የድሮ ስርአት ነፍጠኞች ያሁኑ አገር ባይበጠብጡ ይሻላል።”
ወ/ሮዋ አክላም ” ትልልቅ አዋቂ ሰዎች የመለስ አይምሮ ያፈለቀውን ራእይ የሚያስፈፅሙ አሉ ተመርጠው በህዝብ መቶ ድምፅ ተሰጥቷቸ እያሉ አሁን ለምን አገር ይረበሻል? እኔ በእውነቱ ከሆነ ለቤተሰብ ለንብረቴ ማሰብ ጀምሬያለሁ። እርግጠኛ ነኝ ብዙዎች እንደኔው ማሰብ መስጋት ጀምረዋል። ጥሩ አይደለም ሰላም እና መረጋጋት ያስፈልጋል በመጀመሪያ።” ብላለች::
ስለ ባሏ ራዕይ ከሞተ በኋላም እንዲነገር የምትፈልገው ወይዘሮ አዜብ ሕዝብ የመለስን ፓርክ በማቃጠሉ የተሰማትን ስሜት ስትገልጽም “የመለስ እሚያህል ትልቅ ሰው በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ እማይታወቅ ሰው፣ ከዚህ በፊትም እንዳልኩት በፔሮል የሚተዳደር ፕሬዚደንት በሶስት ሺህ ብር ደሞዝ የትም አለም የለም። እና ዛሬ ለመታሰቢያ አንድ ፓርክ ቢሰራ እነዚ ሰልፍ ወጡ የተባሉ አደገኛ ቦዘኔዎች አቃጠሉ አሉ። ሀዘኔ መሪር ነው በእውንት ከሆነ። መለስ ቢያየን ያፍርብናል። ራእይ ሰጥቶን ያ ሁሉ አይምሮ ጨምቆ አውጥቶ እኛ እንዲ ወደ ድንቁርና ስንሄድ ያሳዝነዋል። በቶሎ መንግስ ፀጥታ ሊያስከብር ይገባዋል። እነዚ ቦዘኔዎችም ለፍርድ መቅረብ አለባቸው።” ብላለች::
የቀድሞው ጠ/ሚ/ር ባለቤት ወ/ሮ አዜብ መስፍን የሰሞኑ ሕዝባዊ ቁጣ ለቤተሰቧና ለንብረቷ እንድታስብ ካደረጋት ቀጣይ እቅዷ ገንዘቧን አሽሽታ ወደ ሌላ ሃገር መፈርጠጥ? ይህ የሕዝብ ጥያቄ ነው::